Articles
በኢትዮጵያ የአራት ብሔራውያን ክልላውያን መንግሥታት የሕዝብ መዝሙሮች ይዘት ትንተና
- Journal ZENA - LISSAN (Journal of Academy of Ethiopian Languages and Cultures)
- Issue Vol 27 No 1 (2018): ZENA-LISSAN (Journal of Academy of Ethiopian Languages and Cultures)
- Published
- ISSN 2222-6028
Abstract
“የኢትዮጵያን ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የመሠረቱት” ብሔራውያን ክልላውያን መንግሥታት
በየሕገ መንግሥታቸው የየራሳቸው የሕዝብ መዝሙር እንደሚኖራቸውና በሕዝብ መዝሙሮቻቸው
ሊንፀባረቁ የሚገባቸውን ይዘቶች ደንግገዋል፡፡ ድንጋጌያቸውን ተግባራዊ በማድረግ የራሳቸው ክልል
ሕዝብ መዝሙር ያላቸው የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣ የዐማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣
የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥትና የሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ብቻ ናቸው፡፡ የዚኽ ጥናት
ትኩረትም በተጠቀሱት ብሔራውያን ክልላውያን መንግሥታት የሕዝብ መዝሙሮች ላይ ነው፡፡ ይኽን
ጥናት ማካኼድ ያስፈለገበት ምክንያት፣ በብሔራውያን ክልላውያን መንግሥታት የሕዝብ መዝሙሮች ላይ
የተደረገ ጥናት አለመኖርና ክፍተቱን ለመሙላት ምርምር ማድረግ አስፈላጊ በመኾኑ ነው፡፡ የጥናቱ ዐቢይ
ዓላማ የአራት ብሔራውያን ክልላውያን መንግሥታት የሕዝብ መዝሙሮች የሀገራችንን ታሪካዊ፣
ፖለቲካዊና ባህላዊ ኹኔታዎች ምን ያኽል እንዳንጸባረቁና በኅብረተ ሰቡ ውስጥ ለማስረጽ የተደረገውን
ጥረት መመርመርና ይዘቶቹን መተንተን ነው፡፡ ከዚኽ ዐቢይ ዓላማ የሚመነጩ ዝርዝር ዓላማዎችም፣
ብሔራውያን ክልላውያን መዝሙራቱን ለመድረስ ያነሣሡ ታሪካዊና ፖለቲካዊ ምክንያቶችን መመርመር፣
ብሔራውያን ክልላውያን መንግሥታት በየሕገ መንግሥታቸው ስለብሔራዊ ክልላቸው የሕዝብ መዝሙር
የደነገጓቸው ይዘቶች ምን ያኽል በየመዝሙሮቹ እንደተንጸባረቁ መመርመር፣ መተንተን፣ የሕዝብ
መዝሙሮቹ ብሔራዊ ማንነትን ለመገንባት (ለማጠናከር) (national identity building and
strengthening) እንዲሁም ሀገራዊ አንድነትን ለማጎልበልበት ያላቸውን ጠቀሜታ፣ ብሔራውያን
ክልላውያን የሕዝብ መዝሙራቱ ከፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ኢትዮጵያ ብሔራዊ መዝሙር ጋር
እንዴት ተጣጥመው አገልግሎት እንደሚሰጡ መፈተሽና የሕዝብ መዝሙሮቹ የሚገልጹዋቸውን ርዕዮተ
ዓለሞች መመርመር የሚሉት ናቸው፡፡ እነዚኽን ዓላማዎች ለማሳካት ጥናቱ የሚመልሳቸው ጥያቄዎች፡-
ብሔራውያን ክልላውያን መዝሙሮቹን ለመድረስ ያነሣሡ ምክንያቶች ምን ምን ናቸው? ብሔራዊ ክልላዊ
መዝሙሮቹ የተደረሱበትን ፖለቲካዊ፣ ታሪካዊና ማኅበራዊ እውነታ ምን ያኽል አንጸባርቀዋል?
በብሔራውያን ክልላውያን ሕገ መንግሥታት ስለሕዝብ መዝሙሮች የተደነገጉት ይዘቶች በሕዝብ
መዝሙሮቻቸው እንዴት ተንጸባረቁ? በብሔራውያን ክልላውያን የሕዝብ መዝሙሮች አማካይነት
በወጣቶች አዕምሮ እንዲሰርፁ የተደረጉትን ርዕዮተ ዓለሞች ብሔራዊና ሀገራዊ ጠቀሜታ ምን ያኽል ነው?
የሚሉት ናቸው፡፡ ጥናቱ፣ በተጠቀሱት ብሔራውያን ክልላውያን የሕዝብ መዝሙሮች ላይ ማተኰሩ
የተለያዩ ጠቀሜታዎች አሉት፡፡ የብሔራውያን ክልላውያን መዝሙራቱ ታሪክ ምን እንደሚመስል
ለመገንዘብ፣ የብሔራውያን ክልላውያን መዝሙራቱን ተግባርና አገልግሎት ለመረዳት በተለይም የብሔራዊ
ማንነትን ለመገንባት (national identity building and strengthening) ያላቸውን ሚና፣
(በብሔራውያን ክልላውያን የሕዝብ መዝሙሮች አማካይነት በወጣቶች አዕምሮ እንዲሰርፁ የተደረጉትን
ርዕዮተ ዓለሞች ለመረዳት ያስችላል፡፡) ሀገራዊ አንድነትን ለማጠናከርና ለማጎልበት ያላቸውን ጠቀሜታ፣
እንዲሁም ብሔራዊ ክልላዊ መዝሙራቱ ከፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ኢትዮጵያ ብሔራዊ
መዝሙር ጋር እንዴት ተጣጥመው አገልግሎት እንደሚሰጡና በየሕገ መንግሥታቸው የሕዝብ
መዝሙሮቻቸው እንዲንጸባረቁ የተደነገጉት ይዘቶች እንዴት እንደተንጸባረቁ ለመረዳት ያስችላል፡፡
እንዲሁም፣ ወደ ፊት ለሚደረጉ ተመሳሳይ ጥናቶች መነሻነት ያገለግል፡፡ የዚኽ ጥናት የመረጃ ምንጮች
ጥናቱ ትኩረት ያደረገባቸው ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥታት ሕገ መንንግሥቶች፣ የብሔራዊ ክልላዊ
መንግሥታት የሕዝብ መዝሙሮች፣ ዐዋጆች፣ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥቱን የሚመሩት