Articles
የደቂቀ እስጢፋኖስ ዐውደ ንባባዊ ትንታኔ
- Journal ZENA - LISSAN (Journal of Academy of Ethiopian Languages and Cultures)
- Issue Vol 27 No 1 (2018): ZENA-LISSAN (Journal of Academy of Ethiopian Languages and Cultures)
- Published
- ISSN 2222-6028
Abstract
የዚህ ጥናት ትኩረት ደቂቀ እስጢፋኖስ(“በህግ አምላክ”) በሚል ርዕስ በጌታቸው ሀይሌ ከግዕዝ
ወደ አማርኛ ተተርጉሞ ለሁለተኛ ጊዜ በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ ፕሬስ የታተመ መጽሀፍ ነው።
የአባ እስጢፋኖስና የተከታዮቻቸው ገድል በጥቅሉ ደቂቀ እስጢፋኖስ ተብሎ አራት ገድሎችን
በአንድ ጥራዝ አካቶ ለህትመት በቅቷል። የጽሁፉ ዋና አላማ ደቂቀ እስጢፋኖስን በዐውደ ንባባዊ
ስልት መተንተን ይሆናል። በደቂቀ እስጢፋኖስ ገድል ውስጥ የተካተቱት ገድሎች የ15መ/ክ/ዘ
ኢትዮጵያዊያን በተለይም የሃይማኖት መጻህፍትን በማንበብ በመጻፍ እና በመመራመር የላቀ
አስተሳሰብ እንደነበራቸው የሚጠቁሙ ናቸው። አባ እስጢፋኖስ እና ተከታዮቻቸው ከአጼ
ይስሀቅ ጀምሮ እስከ አጼ ናኦድ ድረስ በነበረው ንትርክ ከደረሰባቸው መከራ ተነስተው
ገድላቸውን የጻፉት ተከታዮቻቸው ናቸው። በገድላቸው ውስጥ የምናየው በዘመኑ የነበረውን
የማሰብ ነጻነት ጠቋሚ አሻራዎች ነው። ይህም ጥናት በአውደ ንባባዊ ስልት ገድሉ ውስጥ የተነሱ
ኮዶችን በማፍታታት “ሀሳብን በሀሳብ እና ሀሳብን በስልጣን መርታት” የሚል አብይ ጭብጥ
ተለይቶ ወጥቶለታል። የአባ እስጢፋኖስና የተከታዮቻቸው ገድሎች እንደ ሌሎች ገድሎች ዐውደ
ንባቦቹ የሃይማኖት ናቸው። በአውደ ንባቦች ውስጥ ያሉት ድርጊቶች ሁነቶች እና ሁኔታዎች
ሃይማኖታዊ ናቸው። ሆኖም በእምነት አይን አይተን በእምነት ጆሮ ሰምተን በእምነት ልቡና
አምነን ይሁን ብለን የምናስተናግደው ብቻ አይደሉም። ስለዚህ ደቂቀ እስጢፋኖስ ከገድልነቱ እና
ከስነጽሁፍ ቅርስነቱ ባሻገር በተለያየ የሙያ መስክ ቢጠና፣ ማስረጃዎችን ለይቶ በማውጣት
ለሌሎች የጥናት መስኮች ግብአት በመሆን ያገለግላል።